የከተማ ልማትና መልካም አስተዳደር ፕሮግራሞች
የስድስት ወር ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ ተካሄደ
የሥራና ከተማ ልማት ሚኒስቴር ከክልሎች ጋር በቋሚነት በየሶስት ወሩ የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማና የምርጥ ተሞክሮ ልውውጥ ያደርጋል፡፡ በዕቅድ አፈጻጸም ላይ ባጋጠሙ ችግሮች ዙሪያም በስፋት ይወያያል፡፡ ለችግሮቹም በጋራ የመፍትሔ ሐሳቦችንም ያስቀምጣል፡፡ በዚሁ መሰረት የ2001 በጀት ዓመት የግማሽ ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ የተሞክሮ ልውውጥ ከጥር 25-27 ቀን 2001 ዓ.ም. የክልል ሥራና ከተማ ልማት፣ የንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊዎች፣ የቤት ልማት ፕሮጀክት ጽ/ቤት ኃላፊዎችና ጉዳዩ የሚመለከታቸው የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት በአዲስ አበባ ተካሂዷል፡፡ በመድረኩ ላይ የመወያያ አጀንዳ ሆነው የቀረቡት የተቀናጀ የቤቶች ልማት ኘሮግራም የግማሽ በጀት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀም እና በተለይ ባለፉት ሁለት ዓመት በጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ልማት ፕሮግራምና የከተሞች መልካም አስተዳደር ፕሮግራም ዙሪያ የተገኙ መልካም ተሞክሮዎች ጥናት ናቸው፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ የጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ልማት ኘሮግራም መልካም ተሞክሮ ተቀምሮ ለውይይት ቀርቧል፡፡ የከተሞች መልካም አስተዳደር ማሻሻያ ፕሮገራምን አፈጻጸም ለማስፋፋት የሚያስችል አቅጣጫም በዚሁ ጊዜ ለውይይት ቅርቦ ገንቢ አስተያየቶች ተስጥቶበታል፡፡
የተቀናጀ የቤቶች ልማት ኘሮግራም በአዲስ አበባ ከተማ ከ1996 ዓ.ም. በሌሎች ክልል ከተሞች ደግሞ ከ1999 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ በመደረግ ላይ የሚገኝ ሀገር አቀፍ ኘሮግራም ሲሆን የኘሮግራሙ ዋና ዓላማ በከተሞች የሚታየውን የመኖሪያ ቤት እጥረት ማቃለል፣ ለከተማ ነዋሪው ሰፊ የሥራ ዕድል መፍጠር፣ ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል እንዲኖር ማድረግ፣ አገራዊውን የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ አቅም መገንባት እንዲሁም ክህሎትና ሙያን ማዳበር ነው፡፡
እነዚህን ዓላማዎች ለማሳካት የተጀመረው የተቀናጀ የቤቶች ልማት ፕሮግራም በአገር አቀፍ ደረጃ መተግበር ከጀመረ ሁለት ዓመታት ብቻ የተቆጠሩ ቢሆንም በዚህ ጥቂት ጊዜ ውስጥ በርካታ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳዎችን አስገኝቷል፡፡ በ1999 በጀት ዓመት ግንባታቸው የተጀመሩ ቤቶች አብዛኛዎቹ በመጠናቀቅ ላይ የሚገኙ ሲሆን የተወሰኑት ደግሞ ለነዋሪዎች ተላልፈዋል፡፡ በ2000 በጀት ዓመት የተጀመሩትም በተሻለ የአፈጻጸም አቅም ግንባታቸው በመካሄድ ላይ ሲሆን በ2001 የበጀት ዓመት ደግሞ ከ1999 ጀምሮ ግንባታቸው ተጀምሮ በሥራ ተቋራጮችና በግንባታ ግብዓት እጥረት፣ ከሥራው ስፋትና ውስብስብነት እንዲሁም ከማስፈፀም አቅም ማነስ ጋር በተያያዘ ያልተጠናቀቁትን ጨምሮ የ100 ሺህ የጋራ መኖሪያ ቤቶቸ ግንባታ በመካሄድ ላይ ይገኛል፡፡
በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ አጋማሽ ዓመት በኦሮሚያ፣ በትግራይ፣ በአማራ፣ በደቡብ ብ/ብ/ህ እና በሐረሪ ክልሎች እንዲሁም በአዲስ አበባ፣ በድሬዳዋ ከተሞች ሰፊ የቤቶች ግንባታ ሥራ ተከናውኗል፡፡ ቤቶች ለተጠቃሚዎች በማስተላለፍ ረገድም በሁሉም ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች ሰፊ ሥራ ተሰርቷል፡፡ በተለይም በአዲስ አበባ በሦስተኛው ዙር ዕጣ ለወጣላቸው 11,000 ተመዝጋቢዎች ቤት የማስተላለፍ ሥራ ተከናውኗል፡፡ ልዩ ድጋፍ በሚሹ ክልሎችም ሊሠሩ የታቀዱት የ500 ቤቶች ግንባታ የቅድመ ዝግጅት ሥራ በስፋት በመከናወን ላይ ይገኛል፡፡
የእንዲህ ዓይነቱ መጠነ ሰፊ የሆነ ቤቶች ልማት ፕሮግራም በአገራችን አዲስ በመሆኑ ዕቅዱን ለማስፈጸም ወደ ሥራ በተገባበት ወቅት ያጋጠሙ ችግሮችን ደረጃ በደረጃ በመፍታት ዕቅዱን ከግብ ለማድረስ ከፍተኛ ርብርብ ተደርጓል፡፡ በሥራ ሂደት ያጋጠሙ ችግሮችን በዘለቄታው ለመፍታት በርካታ የአቅም ግንባታ ሥራዎች የተከናወኑ ሲሆን በዚህም ተጨባጭ ውጤት ተገኝቷል፡፡ ለአብነት ያህል በመጀመሪያ ላይ የነበረውን የሥራ ተቋራጮችና አማካሪዎችን እጥረት ለማስወገድ የአቅም ግንባታ ሥራ በስፋት በመከናወኑ በአሁኑ ጊዜ በቂ የአገር ውስጥ የሥራ ተቋራጮችንና አማካሪዎችን ለማፍራት ከመቻሉም በላይ ከቤቶች ልማት አልፎ የመንግሥት የግንባታ ፕሮጀክቶችን ለመሥራት የሚያስችል አቅም ተፈጥሯል፡፡ ነባር የሥራ ተቋራጮችም ገልባጭ ተሽከረካሪዎችን በብድር የሚገዙበትና ልዩ ልዩ ሥልጠናዎች የሚያገኙበት ሁኔታ በመመቻቸቱ የመፈጸም አቅማቸው ከፍ ብሏል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ለቤት ልማት ኘሮግራሙ አጋዥ የሚሆኑ ጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት በበቂ ሁኔታ ለማፍራት ተችሏል፡፡ ከቤት ልማት ጋር በተያያዘ ብቻ ፕሮግራሙ ከተጀመረ ጊዜ ወዲህ 4,000 የሚሆኑ የጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርኘራይዞች ወደ ሥራ ገብተዋል፡፡
በሌላም በኩል በኘሮግራሙ ትግበራ ወቅት የታዩትን ቁልፍ የአቅርቦት፣ የትራንስፖርትና የግንባታ አቅም ውስንነትን ለማቃለል የሚያስችሉ ኘሮጀክቶች ተቀርጸው ተግባራዊ ተደርገው አመርቂ ውጤት አስገኝተዋል፡፡ በተለይም በትራንስፖርት በኩል ከወደብ ወደ ተርሚናሎችና ከተርሚናሎች ወደ ግንባታ ሳይቶች የግንባታ ቁሶችን ለማድረስ የነበረውን የአቅም ውስንነት ለመፍታት እያንዳንዳቸው 40 ቶን የመጫን አቅም ያላቸው የጭነት ተሽከርካሪዎች ከውጭ በማስገባት ሥራ ላይ እንዲውሉ በመደረጉ እጥረቱ ተቃልሏል፡፡ በአጠቃላይ በቤቶች ልማት ኘሮግራም እስካሁን የተገኙትን ውጤቶች ይበልጥ ለማጠናከር ከ2000 በጀት ዓመት ጀምሮ በመተግበር ላይ ያሉትን የአቅም ግንባታ ሥራዎች ወደላቀ ደረጃ የማድረሱ ጉዳይ አሁንም ልዩ ትኩረት እንዲሰጠው በመድረኩ ላይ መግባባት ተደርሶበታል፡፡
ሌላው በዚሁ መድረክ ውይይት የተካሄደበት ቁልፍ ሥራ የጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ልማት ኘሮግራምን ይመለከታል፡፡ በመተግበር ላይ ያለው የጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርኘራይዝን መስፋፋት በብዙ መቶ ሺዎች ለሚቆጠሩ ወጣቶች፣ ሴቶችና ሌሎች የዘርፉ ተሳታፊዎች የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም ባሻገር የሃብትና የክህሎት ባለቤት ለመሆን አብቅቷቸዋል፡፡ በ2001 የመጀመሪያ መንፈቅ ዓመትም ኘሮግራሙን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ ባላፉት ዓመታት የተገኙትን በጐ ተሞክሮዎችን በመቀመር በቀሪው የሁለት ዓመት የኘሮግራም ዘመን በሁሉም አካባቢዎች በተሟላ ሁኔታ ተፈፃሚኒት እንዲኖራቸው ለማድረግ የሚያስችሉ ሥራዎች ተከናውነዋል፡፡ በዚህም መሠረት በኘሮግራሙ አፈፃፀም የተገኙ መልካም ተሞክሮዎች የመለየትና የመቀመር ጥናት ተከናውኖ የተሻሉ ተሞክሮዎች ያጠቃለለና እነዚህን ተሞክሮዎች ይበልጥ ለማጠናከርና በሁሉም አካባቢዎች ለማዳረስ የሚቻልበትን ሥልት እና ዝርዝር የማስፈፀሚያ ዕቅድ የያዘ ሠነድ ተዘጋጅቶ በውይይት ዳብሯል፡፡ በሥራና ከተማ ልማት ሚኒስቴርና በክልሎች መድረክ ላይም በሠነዱና በቀጣይ ሥራዎች ላይ ውይይት ተካሒዷል፡፡ ስለሆነም መልካም ተሞክሮዎቹ ተፈፃሚነታቸው ይበልጥ እንዲሰፋ በማድረግ የኘሮግራሙን ውጤታማነት ይበልጥ ለማሳደግ በቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ እንዲሆን ውሳኔ አግኝቷል፡፡
የከተሞች መልካም አስተዳደር ፕሮግራምን አስመልክቶ በተደረገው ውይይት ፕሮግራሙ በየከተሞቹ ለውጥ በማምጣት ላይ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ በኘሮግራሙ ትግበራ ወቅት በየአካባቢው የታዩ የተሻሉ ልምዶችን እና ኘሮግራሙን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግና መልካም ተሞክሮዎችን ለማጠናከርና በሁሉም አካባቢዎች ለማዳረስ የሚቻልበትን ስልት ባካተተው የጥናት ሠነድ ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጓል፡፡ በቀጣይም የተቀመሩትን መልካም ተሞክሮዎች ሰፊ ተፈፃሚነት እንዲኖራቸውና በዚህም በመልካም አስተዳደር ዙሪያ ከፍተኛ ለውጥ ለማምጣት ከፌዴራል እስከ ከተማ ድረስ ያሉት አካላት ትኩረት ሰጥተው እንዲንቀሳቀሱ በመድረኩ ተወስኗል፡፡
|